ኮንትሮባንዲስቶች እነማን እንደሆኑ ለፓርላማው በግልጽ እንዲናገሩ የገቢዎችና ጉምሩክ ኃላፊዎች ተጠየቁ

  • ኃላፊዎቹ ጥያቄውን አልመለሱም

የአገሪቱን ኢኮኖሚ ከመጉዳት ባለፈ የፖለቲካ ቀውስ እየፈጠሩ

ናቸው የሚባሉ ‹‹ኮንትሮባንዲስቶች›› ማንነት በግልጽ

ለፓርላማው እንዲቀርብ፣ የፓርላማው አባላት ከፍተኛ ጥረት

ቢያደርጉም ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡

የፓርላማው አባላት በከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች ሳይቀሩ በአገሪቱ ለሚታየው የፖለቲካ ቀውስ ጣታቸውን የሚቀስሩት ‹‹ኮንትሮባንዲስት›› በተባሉ ማንነታቸው በማይታወቅ ኃይሎች ላይ ስለሆነ፣ የእነዚህን ማንነት ፓርላማው በግልጽ የማወቅ ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ ማንነታቸው እንዲገለጽላቸው የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን አመራሮችን ጠይቀዋል፡፡

የፓርላማ አባላቱ ጥያቄውን ያቀረቡት ማክሰኞ ጥር 22 ቀን 2010 ዓ.ም. የግማሽ ዓመት የሥራ አፈጻጸማቸውን ሪፖርት ለማድረግ ፓርላማው ለተገኙት፣ ለባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሞገስ ባልቻና ሌሎች አመራሮች ነበር፡፡

አንድ የፓርላማ አባል፣ ‹‹ስሙ የማይጠራው ኮንትሮባንዲስት ማነው?›› ሲሉ በስላቅ ጠይቀዋል፡፡ በአገሪቱ የብሔር ግጭት እየፈጠሩ ያሉት እነዚህ ኮንትሮባንዲስት የሚል ስም የወጣላቸው በኔትወርክ ተሳስረው የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች እንደሆኑ የጠቆሙት ሌላ የምክር ቤቱ አባል ደግሞ፣ ‹‹በእነዚህ ኃይሎች ጡንቻ ገቢዎችና ጉምሩክ ራሱ ታስሯል፤›› ሲሉ ተችተዋል፡፡

በተለይ በጉምሩክ ቅርንጫፎች ላይ የሚመደቡ የሥራ ኃላፊዎች ለዚሁ ሕገወጥ ሥራ እንዲመቹ ሆነው የሚመለመሉ መሆኑን፣ በዚህም የተነሳ በአሁኑ ወቅት አንድ ብሔር ነጥሎ የማጥቃት ግጭት እንዲፈጠር ምክንያት ሆነዋል ሲሉ እኚሁ የምክር ቤት አባላት ወቅሰዋል፡፡

በአገሪቱ የወጪ ንግድ መስመሮች በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች በድንገት የኤሌክትሪክ ኃይል ተቋረጠ ማለት ኮንትሮባንድ የጫኑ ተሽከርካሪዎች እያለፉ እንደሆነ በገሃድ የሚታወቅ መሆኑን የጠቀሱ ሌላ የምክር ቤት አባል፣ በዚህ ኔትወርክ ውስጥ የተቋሙ ሠራተኞች ሊኖሩ እንደሚችሉ ያሳያል ብለዋል፡፡

የባለሥልጣኑ የሥራ ኃላፊዎች የግማሽ ዓመት ሪፖርት በርካታ ጉዳዮችን የዳሰሰ ቢሆንም፣ ኮንትሮባንዲስቶችን በተመለከተ የተነሳው ጥያቄ አመዛኙን ጊዜ የያዘ ነበር፡፡

ለተነሳው ጥያቄ በቅድሚያ ምላሽ የሰጡት የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተርና የሕግ ማስከበር ዘርፍ ኃላፊ አቶ ዘመድ ተፈራ ሲሆኑ፣ የኮንትሮባንዲስቶቹን ማንነት መግለጽ የሚቻል ቢሆንም የሚወሰደውን ዕርምጃ መጠበቅ የተሻለ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡

‹‹በከፍተኛ የፖለቲካ አመራሩ ኮንትሮባንድን ለመዋጋት ቁርጠኝነት በመታየቱና ለይተን እንደናቀርብ በታዘዝነው መሠረት ቀንደኞቹን በጥናት ለይተን በአገር አቀፍ ደረጃ ለተቋቋመው ግብረ ኃይል አቅርበናል፤›› ያሉት አቶ ዘመድ፣ ‹‹እከሌ እከሌ ብሎ ማቅረብ ይቻላል ነገር ግን የሚወሰደውን ዕርምጃ በጋራ ብናይ ይሻላል፤›› ብለዋል፡፡

የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው በፓርላማ አባላቱ እንደተነሳው ኮንትሮባንዲስቶቹ የራሳቸው መጋዘን ያላቸው፣ በኔትወርክ የተደራጁና ተግባራቸውም በአሁኑ ወቅት አሳሳቢ የሚባል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ይኼንን መበጣጠስ ካልተቻለ ከኢኮኖሚ ጉዳቱ በላይ የፖለቲካ ቀውስ የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ የአገሪቱ የፖለቲካ አመራር በጉዳዩ ላይ ቁርጠኛነቱን ያሳየ በመሆኑ፣ ዕርምጃ ይወስዳል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ በግማሽ ዓመት ውስጥ 331.6 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ ንብረቶች በኮንትሮባንድ ሊገቡ ሲሉ የተያዙ መሆኑን፣ 105.3 ሚሊዮን ብር የሚገመት ንብረት ደግሞ ሊወጣ ሲል መያዙ ተገልጿል፡፡


Source: https://www.ethiopianreporter.com/article/6836

Leave a comment

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.